Breaking News
Home / Amharic / የኦሮሞው መንግስት የአማርኛና የታሪክ ትምህርት አገደ።

የኦሮሞው መንግስት የአማርኛና የታሪክ ትምህርት አገደ።

የደብረብርሃን ዩንቨርስቲ ጉዳይ በዝርዝር!

• የአማርኛ ቋንቋ ትምህርት “ተዘጋ”;
• አጼ ዘርዓ ያዕቆብ የመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ታሪክ ጥናት “ተዘጋ”
• የባህል ጥናት ማዕከል “ተዘጋ”
• ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ:- The first and only university in Ethiopia and the world to officially close Amharic Language and Literature department!
• በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ከቋንቋ፣ ከማንነት፣ ከታሪክ፣ ከባህልና ከአገርበቀል ዕውቀቶች ጋር የተያያዙ የትምህርት መስኮች እንዲዘጉ መወሰኑ;

1. መነሻ
ዩኒቨርሲቲው ማስተማር የጀመረው በማኅበራዊ ሳይንስ፣ በተፈጥሮ ሳይንስና በሥነ ትምህርት ክፍች ነበር፡፡ በዚህም ብዙ ሺህ ተማሪዎች አስተምሮ አስተምሮ አስመርቋል፡፡ የአካባቢው ማኅበረሰብም ብዙ ርቀው ሳይሄዱ በመረጡት የሙያና የትምህርት መስክ ለመማር እድል አግኝቶ ቆይቷል፡፡ ዛሬ ግን ይህ መብት ባልታወቀ ምክንያት ተጥሶ የአካባቢው ወጣቶችና ጎልማሶች በመረጡት የትምህርት መስክ እንዳይማሩ እንዳይሰለጥኑ፣ እውቀትና ክህሎቶች እንዳይኖራቸው ህገ-ወጥ በሆነ መንገድ ተወስኖባቸዋል፡፡ ሌሎች የሃገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች ማኅበራዊ ሳይንስን ማለትም ታሪክ፣ አማርኛ ቋንቋና ሥነ ጽሑፍ፣ ጂኦግራፊ፣ ሶሲዮሎጂ፣ ሳይኮሎጂ፣ ጋዜጠኝነት፣ ፖለቲካ ሳንስ ወዘተ እያስፋ በማስተማር በፒ.ኤች.ዲ ደረጃ እሰለጠኑ ባለበት ሁኔታ፤ ደ/ብ/ዩ የሚማሩ በርካታ ተማሪዎች እያሉ፣ ተመራጭ ሆኖም ሳለ፣ የሚያስተምሩ በርካታ መምህራንም እያሉ፣ የማኅበረሰቡም የመማር ፍላጎት በከፍተኛ ደረጃ እያለ ለምን እንዲዘጉ ተደረገ?
• የሸዋ ታሪክ፣ ባህል፣ መልክዓ ምድር፣ የአማርኛ ቋንቋን፣ ሀገር በቀል እውቀትን፣ ኪነ ጥበቡን ማን ያጥናቸው? የአካባቢው ወጣቶችና ተማሪዎች እንዲዘጉ በተወሰነባቸው በእነዚህ የትምህርት መስኮች ለመማርና ለመሰልጠን ለምን ይከለከላሉ?
• ክልሎች የራሳቸውን ባህል፣ ታሪክ፣ ቋንቋ የመማር፣ የማሳደግ መብት እንዳላቸው ደንግጓል፡፡ እውነታው ይህ ሆኖ እያለ የደ/ብ/ዩ አመራር ግን ይህንን መብት ነው የደፈጠጠው በምን ስልጣኑ ነው?
• ሸዋ በኢትዮጵያ ታሪክ ፖለቲካ ባህልና ኪነጥበብ በርካታ ፋና ወጊ ሊቃውንት የፈለቁበት፤ ሃገር ያጸኑ፣ ሕይወታቸውን ለሃገር እድገትና አንድት የሰጡ ናቸው፤ አጼ ዘርዓ ያዕቆብ፣ አጼ ምኒልክ፣ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ፣ ተክለ ሐዋርያት ተክለ ማርያም፣ መኮንን እንዳልካቸው እና ሌሎች አያሌ ይጠቀሳሉ፡፡ ይህም አካባቢው ቋንቋ፣ ዲፕሎማሲ፣ ታኩ በተለይ የመካከለኛው ዘመን ታሪክ፣ ማኅበረሰባዊ ጥናት፣ ሃገር በቀል እውቀቱ፣ ኪነ ጥበቡ፣ የትውልድ ቅብብሎሹ ይጠና ዘንድ ትልቅ መነሻ ሃብት ነው፡፡ ከዚህ የታሪክ ቁርኝት በግድ ተነጥሎ ከቋንቋ፣ ባህልና መሰረታዊ ሳይንስ ጋር የተያያዙ ትምህርቶችን መዝጋት ከእውነትና ከሕዝብ ጋር መጋጨት ከመሆኑም በላይ ተጠያቂ የሚያደርግ ነው፡፡
• ይህ ሁሉ ነገር የሚደረገው ይህ ነው የሚባል መሰረታዊ ጥናት ሳይደረግ በጥቂት አመራች ፍላጎትና ግላዊ ውሳኔ መሆኑ ሲጨመርበት ድርጊቱን ኢ-ፍትሃዊና ኢ-ሳይንሳዊ ያደርገዋል፡፡ መምህራን አልተወያዩም፣ ተማሪዎች አልተወያዩም፣ ማኅበረሰቡ እንደባለድርሻ አካል ሃሳቡ አልተጠየቀም፣ ይፋዊ ጥናትም አልተደረገም፡፡

2. ‹ዲፈረንሼሽን›
‹ዲፈረንሼሽን›፣ ‹ሴንተር ኦፍ ኤክሰለንስ›ና ‹አፕላይድ ዩኒቨርሲቲ› በአሁኑ ወቅት በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ያለአግባብና ምንነታቸውን በውል ባለመረዳት ወይም እነሱን ሰበብ በማድረግ አደገኛና ድብቅ ዓላማን ለማስፈጸም ጥቅም ላይ እየዋሉ ይገኛሉ፡፡ ከዚሁ ከ‹ዲፈረንሼሽን› (የትኩረት መስክ ልየታ) ጋር በተያያዘ ያለበቂ ጥናት፣ ያለአሳማኝ ምክንያት እና የዩኒቨርሲቲው መምህራንና ሰራተኞችም ሆነ ባለድርሻ የሆነው የአካባቢው ማኅበረሰብና የማኅበረሰብ መሪዎች ሳይመክሩበት በጥቂት የከፍተኛ አመራር አባላት የተሸፋፈነ ውይይትና ውሳኔ ሰጭነት ምክንያት በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ከማንነት፣ ከታሪክ፣ ከባህል፣ ከቋንቋና ከአገርበቀል ዕውቀቶች ጋር የተያያዙ የማህበራዊና የተፈጥሮ ሳይንስ የትምህርት መስኮች እንዲዘጉ መወሰኑ አግባብ ካለመሆኑም በላይ ከፍተኛ ትምህርታዊ፣ ማንነታዊ፣ አብርሆታዊና ማኅበራዊ ቀውስን የሚጋብዝ መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡
አንድ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም አገልግሎቱን ከሌሎች ተፎካካሪ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በተሻለና በተለየ ሁኔታ ሳቢ አድርጎ በማቅረብ ላይ የሚያተኩረውን ‹ዲፈረንሼሽን› ወይም ‹ልየታ› የተባለውን ሃሳብ አሳስቶ በመረዳት ወይም ሆነ ብሎ የግልንና የቡድንን ጥቅም ለማስፈጸም አስቦ በመንቀሳቀስ የትምህርት ክፍሎችንና ኮሌጆችን መዝጋት በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የተያዘ እንቅስቃሴ ሆኗል፡፡ ከዓለም የከፍተኛ ትምህርት ልምድ ለመገንዘብ እንደሚቻለው በዕቅድና ስትራቴጂያዊ አካሄድ የሚከተል መሆን ሲገባው ተቋሙ ከ‹ዲፈረንሼሽን› ዓላማ በተሳሳተ አቅጣጫ ርቆ በመሄድ ላይ ይገኛል፡፡
ዩኒቨርሲቲው ሲቋቋም ጀምሮ ለ16 ዓመታት በስራ ላይ ያሉትን የማህበራዊ ሳይንስና ተፈጥሮ ሳይንስ የትምህርት ዘርፎች ከነ መምህራናቸው፣ ከነአስተዳደር ሰራተኞቻቸው፣ ከነ ቤተሙከራቸው፣ እስከ ሦስተኛ ዲግሪ እስከደረሱ መርሐግብሮቻቸው ካለፉት ጥቂት ዓመታት ጀምሮ ለማፈራረስ እየተሄደበት ያለው የተሰላ ዕቅድ ካለፈው ስህተታችን አለመማራችንን የሚያሳይ ሲሆን በቀደመው ሥርዓት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተባረሩ 42 ምሁራንና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተፈጥሯዊ ሞቱን ይሙት በሚል የተፈጸሙትን ደባዎች በአስር እጥፍ አባዝቶ መተግበር አጥፊነቱ እንጂ አልሚነቱ አይታየንም፡፡ ለረጅም ጊዜ የፈሰሰውን ሃብት (በየዓመቱ በቢሊዮን ብር እንደሚመደብ ልብ ይሏል)፣ ጉልበትና ዕውቀት መና የሚያስቀርም ይሆናል፡፡
3. የልዬታ/`differenciation` ወይም የልህቀት ማዕከል መነሾ?
በዓለማቀፍ ዓውድ እንደምንረዳው ልዬታ/`differenciation` ወይም የልህቀት ማዕከል/`centre of excellence` አንድ ተቋም ወይም ዩኒቨርሲቲ የተቋቋመበትን ዓላማ ወይም የተቋቋመበትን አካባቢ እምቅ ሃብት (potential) ማለትም የተፈጥሮ ሃብት፣ በሳይንሳዊ ጥናት ቢለማ እምቅ የሆነ ያልለማ ሃብት፣ አገር በቀል እውቀት ሃብት፣ ባህል፣ የታሪክና አርኬኦሎጂ እምቅ ሃብት፣ የአየር ንብረትና የማኅበረሰብ አኗነዋርና ፍልስፍና ወዘተ ግምት ውስጥ ይገባል፡፡ በመሆኑም ትምህርት ሚኒስር ዩኒቨርሲቲዎች የአካባቢያቸውንና የተቋማቸውን ነባራዊ ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ የትምህርት መስኮችን ለይተው እንዲልኩ ለዩኒቨርሲቲዎች በሰጠው አቅጣጫ መሰረት ዩኒቨርሲቲዎች መርተው በሚልኩበት ወቅት የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ዓላማው ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ ለልህቀት ማዕከልነት የሚያበቃ ተግባራዊ መሰረት የሌላቸው መስኮች ለይቶ ባካተተበት ሁኔታ የአካባቢውን እምቅ የባህልና የቋንቋ ጥናት፣ የመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ታክና አርኬኦሎጂ ጥናት፣ የአገርበቀል እውቀትና ማንነት ጥናት መስኮች ያሉባቸው የማኅበራዊና የተፈጥሮ ሳይንስ ጥናት መስኮችን የልህቀት ማዕከል አድርጎ ካለመምረጡም ባሻገር መስኮቹ “ይዘጋሉ”፣ መምህራኑንም “ትባረራላችሁ” በማለት ኃላፊነት በጎደለው መልኩ በየአደባባዩ በየስብሰባው አመራሩ በተደጋጋሚ ንግግር ሲያደርግ ተሰምቷል፤ ይህም አልበቃ ብሎ በይፋ የጥናት መስኮችን ለመዝጋት የሚረዳ የማስፈጸሚያ ስትራቴጂ ነድፈው ለመዝጋት ውሳኔ ላይ ደርሰዋል፡፡
በነገራችን ላይ አንድ የትምህርት ተቋም የተወሰኑ የተመረጡ መስኮችን የልህቀት ማዕከል አደርጋለሁ የሚል ውሳኔ ይዞም ሆነ ተቋሙ ሲመሰረት ጀምሮ በተመረጡ መስኮች ላይ ብቻ ትኩረት አድርጎ ለመላቅ ሲያልም ሌሎች የትምህርት መስኮችን ይዘጋል ወይም አይሰጥም ማለት አይደለም፡፡ በመረጣቸው መስኮች ላይ ከሌሎች በተለዬ የአካባቢንና የተቋሙን እምቅ ዳራ፣ የሰው ሃብትና አመቺነት በመጠቀም የላቀ ውጤት ለማስመዝገብ እሰራ ነገር ግን በሌሎች መስኮችም መማር ማስተማሩን ያስቀጥላል፡፡ የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ አመራር ድርጊት ግን በዓለማቀፍ አውድም ሆነ በአገራችን ባልተለመደ መልኩ “አልፈለኳቸውም” ያላቸውን መስኮች የልህቀት ማዕከላት ባይሆኑ እንኳ መማር ማስተማር ላይ እንዲቀጥሉ ማድረግ የሚቻልበት አሰራር እያለ በአስደንጋጭ ሁኔታ ለመዝጋት ውሳኔ ላይ ደርሷል፡፡ ተመሳሳይ መመሪያ የተሰጣቸው የአገራችን ዩኒቨርሲቲዎች ከአካባቢያቸው ባህልና እምቅ ሃብት እንዲሁም የተቋማቸው ሁኔታ አንጻር የልህቀት ማዕከላቸውን የመረጡ ቢሆንም ሌሎች መስኮችን ለመዝጋት የሄዱበት የጥድፊያ መንገድ እንደሌለ ለማጣራት ችለናል፡፡
በአገራችን ያለውን ልምድ ብንወስድ፣ የልህቀት ማዕከል ልየታ የሚለው ሃሳብ ከመምጣቱ በፊት ጀምሮ ሃሳቡ ተፈጻሚ የሆነባቸው ተቋማትን እናገኛለን፡፡ ለምሳሌ፡- አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሚታወቀው በውሃ ቴክኖሎጂ ነው፤ ሃረማያ ዩኒቨርሲቲ በግብርና፣ ባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ቴክኖሎጂ (በውሃ፣ በመርከበኝነት/ማሪን ትክኖሎጂ) የሚታወቁ ሲሆን ሌሎችንም መጥቀስ ይቻላል፡፡ አንዳንዶቹ ሲመሰረቱ ጀምሮ ለዚሁ ዓላማ ታስቦ የተቋቋሙ አሉ፣ ለምሳሌ አርባምንጭን መውሰድ ይቻላል፡፡ ይህን የልህቀት ልየታ መተግበር ከጀመሩም በጣም ረዥም ጊዜ ማለትም ለአስርተ ዓመታት የዘለቀ ነው፡፡ ነገር ግን አንዳቸውም ሌሎች የትምህት መስኮችን አልዘጉም፣ እንደውም አዳዲስ መስኮችን፣ ከማኅበራዊ ሳይንስ እስከ ተፈጥሮ ሳይንስ በመክፈት እያስፋፉ ነው፡፡ ብዙ የዓለም ዩኒቨርሲቲዎች በተቋቋሙባቸው ጊዜያት የነበሩ የጥናት መስቻቸውን የሚታወቁባቸው የልህቀት ማዕከላቸው ያደርጋሉ፡፡
የደብረ ብርሃ ዩኒቨርሲቲ ከነባራዊ ሃቅ፣ ከሳይንሳዊ አመክንዮም ሆነ ከሃገር ዓቀፍና ከዓለማቀፍ ተሞክሮዎች ባፈነገጠ መልኩ በጥቂት የአመራር አካላት ፍላጎትና የግል አተያይ በመነሳት ተሞክሮዎችን ከአካባቢው ነባራዊ ሁኔታ ጋር ሳያመሳክሩ ዓላማው ግልጽ ባልሆነና ለተጨማሪ መጠራጠር በሚገፋፋ መልኩ የቋንቋ (ቃል በቃል ፕሬዚዳንቱ `አማርኛን ይዤ አልቀጥልም` ማለቱን ልብ ይሏል)፣ የመካከለኛው ዘመን ታሪክ፣ የባህል፣ የአካባቢው እምቅ የተፈጥሮ ሃብትና አገር በቀል እውቀት ጥናት መስኮችን ለመዝጋት በሚያሳፍር ሁኔታ ውሳኔ ላይ ደርሷል፡፡ ሌላው፤ እነዚህ የትምህርት መስኮች ዩኒቨርሲቲው ሲከፈት ማስተማር የመጀረባቸው መስኮች በመሆናቸው ብዙ የሰው ሃይል፣ ቁሳዊና መንፈሳዊ ሃብት የፈሰሰባቸው ከመሆኑም በላይ አንዳንዶቹ መስኮች በ3ኛ ዲግሪ (ፒ.ኤች.ዲ) ደረጃ ማስተማር የጀመሩ ነበሩ፡፡ ይሄ ሃሳብ የቀደመው አገዛዝ ማኅበራዊ መሰረቶችን ለመናድ የማኅበራዊ ሳይንስ ጥናቶችን `ተፈጥሯዊ ሞታቸውን እንዲሞቱ` የሄደበትን መንገድና በአገረ-መንግስት እሳቤ ላይ የጣለውን ትውልድ ማይረሳው ጠባሳ ለመድገም የሚደረግ መፍጨርጨር እንዳይሆን ያሰጋል፡፡
4. የሸዋ አካባቢ ታሪካዊ ዳራ, የልዬታ ሃሳብ & የአማርኛና ታሪክ መዘጋት
ከላይ እንደተገለጸው ከአሁን በፊት በዓለማቀፍ ዓውድ እንደምንረዳው ልዬታ/`differenciation` ወይም የልህቀት ማዕከል/`centre of excellence` አንድ ተቋም ወይም ዩኒቨርሲቲ የተቋቋመበትን ዓላማ ወይም የተቋቋመበትን አካባቢ እምቅ ሃብት (potential) ማለትም የተፈጥሮ ሃብት፣ በሳይንሳዊ ጥናት ቢለማ እምቅ የሆነ ያልለማ ሃብት እና መሰል ነባራዊ ሃቆችን መሰረት አድርጎ የሚፈጸም ነው፡፡ ለዚህም ጥናት የሚያስፈልገው ሲሆን ከጥናት መነሻዎች ውስጥ አንዱ የአካባቢውን ተፈጥሯዊና ማኅበራዊ መሰረትን መመርመር ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ አካባቢው ምን አለው ተብሎ ሲጠየቅ በጥና የተደገፈ የመካከለኛው ታሪክ ጥናት፣ የአማርኛ ቋንቋና ማንነት ጥናት፣ በተፈጥሮ ሳይንስ መስኮች የሚበለጽጉ እምቅ የተፈጥሮ ሃብት፣ አገር በቀል እውቀት፣ የአካባቢ ማዕከላዊነት፣ የኢትዮጵያ ሃገረ መንግስት ግንባታ እሳቤ የዳበረበት እንደመሆኑ `ይዘጉ` የተባሉት የማህበራና የተፈጥሮ ሳይንስ መስኮች እጅጉን አስፈላጊ ናቸው፡፡ እነዚህ ጥናት መስኮች፤ የአካባቢውን እምቅ ሃብት ለሳይንሳዊ ግብዓት ለመጠቀም፣ ማኅበረሰቡንም ተፈጥሮና ታሪክ ከቸረው ጸጋው የምርምር ተቋዳሽ እንዲሆን ከሁሉም በላይ ቋንቋውን የማበልጸግ፣ ታኩንና ተፈጥሯዊ ሃበቱን የማበልጸግ፣ ማንነቱን የማስጠናት፣ በሃገር በቀል እውቀቱ ሳይንሳዊ ድጋፍ አግኝቶ የመጠቀም ከመንግስት የተፈቀደለትን ህጋዊና በተፈጥሮ ጣገኘውን ፀጋዊ መብቶቹን የሚገፍ ነው፡፡
በጀርመን ሃገር የሚገኘው ሃምቡርግ ዩኒቨርሲቲ ከሚታወቅባቸው የጥናት መስኮች ውስጥ አንደኛው `የኢዮብ ሉዶልፍ የኢትዮጵያ ጥናት ማዕከል/Hiob Ludolf center for Ethiopian Studies` አንዱ ሲሆን የምርምር ትኩረቱን የኢትዮጵያ ጥናት ሆኖ በዋናነት የመካከለኛው ዘመን ላይ ያደረገ ነው፡፡ ለምርምሩ ግብዓት ደግሞ በብዛት የመካከለኛው ዘመን አስኳል ከሆነው ከሸዋ አካባቢ የታሪክ፣ የሥነ ጽሑፍ፣ የግእዝ ቋንቋ፣ የአርኬኦሎጂ፣ የመዛግብት፣ የአገር በቀል እውቀት፣ ባህላዊ ጥበባት እና መሰል ሃብቶችን ይዋሳል፡፡ በዚህ ስራው ጀርመኑ ሃምቡርግ ዩኒቨርሲቲ በዓለም ይታወቃል፡፡ በሸዋ እምብርት ላይ የሚገኘው ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ግን የአካባቢውን ማኅበረሰብ ተፈጥሯዊ መብት በሚገፍና ክብርን በሚነካ መልኩ የመካከለኛው ዘመን ጥናት ያለበትን የአማርና ቋንቋ፣ የማንነት፣ የባህላዊ ጥበባት፣ የታሪክ፣ የሥነ ጽሑፍ፣ የግእዝ ቋንቋ፣ የአርኬኦሎጂ፣ የመዛግብት፣ የአገር በቀል እውቀት እና ሌሎች የኢትዮጵያዊነት አስኳር የሆነ የጥናት መስኮችን ያቀፉ የማኅበራዊ ሳይንስና የተፈጥሮ ሳይንስ መስኮችን በጥቂት አመራች የግል ተነሳሽነት `ለመዝጋት` ውሳኔ ላይ ደርሷል፡፡
ሸዋ በተስፋ ገብረስላሴ አማካኝነት የፊደል ገበታ ቀርፆ አማርኛ ቋንቋን በዘመናዊ መንገድ ለማስተማር ግንባር ቀደም ነው፡፡ አማርኛ ቋንቋ የውቀት ብርሃን ሆኖ በመላው ኢትዮጵያ እንዲሰራጭ ታሪካዊ ድርሻውን ተወጥቷል፡፡ ሸዋ የደራሲያን መንደር ነች፡፡ የጥበብ ጥማት ያለበት ሁሉ ያሻውን ያህል የሚቋደስባት የሥነጽሁፍ ጓደ ናት፡፡ ይህም ሲባል:- ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌን፣ ተስፋ ገብረስላሴን፣ ተክለጻድቅ መኩሪያን፤ መርስኤ ኃዘን ወልደ ቂርቆስን፣ ደጃዝማች ወልደሰማዕት፣ ተክለሐዋሪያት ተክለማርያምን፤ ክቡር ዶክተር ከበደ ሚካኤልን፣ ዳኛቸው ወርቁን፣ ሌሎች አያሌ የሥነ ሰብዕ ታላላቅ ልሂቃንን መጥቀስ ይቻላል፡፡ እነ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ፣ `የአማርኛ ሥነ ትሑፍ አባት` የተባሉትን ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ፣ ብላቴን ጌታ ወ/ጊዮርጊስ ወ/ዮሐንስ፣ አለቃ ኪዳነወልድ ክፍሌ፣ አለቃ ዘነብ ኢትዮጵያዊ፣ ደስታ ተክለ ወልድን፣ አክሊሉ ኃብተ ወልድ፣ መኮንን እንዳልካቸው፣ እንዳልካቸው መኮንን፣ ነጋድራስ ተሰማ እሸቴ፣ ይድነቃቸው ተሰማ፣እና ሌሎች በርካታ ደራስያን፣ የቋንቋ ልሂቃንን የዲፕሎማሲና አስተዳደር ሰዎችን፣ አርበኞችን፣ የታሪክ ባለሙያዎችን የአገር በቀል እውቀት ተመራማሪዎችን፣ የኢትዮጵያ መሰረቶችና ባለውለታዎችን፣ የስልጣኔ ፋናወጊ ሰዎችን ለአብነት መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለሆነም አማርኛ ቋንቋ ትምህርት ክፍል በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ሲከፈትም አንዱ ዓላማው ይህን ታሪካዊ እና ትምህርታዊ እሴት ማስቀጠል፤ የእነዚያን እንቁ የኪነጠበብ ሰዎች የአእምሮ ውጤት ማጥናት እና መዘከር ነበር፡፡ ነገር ግን ይህ እረፍት የነሣቸው ባለሥልጣናት በትውልድ ቀየው ላይ እንኳን መጠጊያ አንፈቅድለት ስለምን ይላሉ?
ከጅምሩ ኮሌጆቹ ሲደራጁም ሆነ በስሩ ያሉ በርካታ ትምህርት ክፍሎች ሲከፈቱ በጥናት ላይ ተመስርተው፣ የአካባቢውንና የሀገርን ፍላጎትን ያገናዘቡ፣ ታሪክን የሚያስጠብቁ፣ ስነ-ልቦናንና ማህበራዊ እሴትን የሚያዳብሩ እንዲሁም የመልማት ጸጋን መሠረት በማድረግ ነበር። ስለሆነም ለእነዚህ ትምህርት ክፍሎች መዘጋት ያበቃቸውን ምክንያት ለመረዳት ለዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች የሚቀርብ ጥያቄ ነው፡፡ ዩኒቨርስቲዎች ሲከፈቱ አንዱ ዓላማ የአካባቢውን ማህበረሰብ በቅርበት ለማገልገል፣ በእውቀት ለማበልጸግ፣ ወጉን፣ ደንቡን፣ ፍላጎቱን በምርምር ለማገዝና ጥያቄዎቹን ለመመለስ ነው።

5. ምን ይጠበቃል?
በግልጽ አነጋገር አማርኛ ቋንቋ የሀገሪቱ ልሳን ነው፡፡ የ120 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን መግባቢያ ነው፡፡ እውነታው ይህ ከሆነ፣ ይህን ሀገራዊ ፋይዳ የማደግፍ የፌደራል ተቋም አስተዋጽኦው ምን ሊሆን ነው? በመሆኑም አማርና ቋንቋ፣ ታሪክ፣ ባህል፣ ሃገር በቀል እውቀት ጥናት እና መሰል ከአካባቢው ማኅበረሰብ ተጨባጭ ሁኔታም ሆነ ከዓለምዓቀፍ አውድ እውነታ ጋር በሚጻረር መልኩ ለመዝጋት የዩኒቨርሲቲው አመራር የወሰነው ውሳኔ የታሪክ ተወቃሽ የሚያደርግና በአስቸኳይ የማስተካከያ እርምጃ ሊወሰድበት የሚገባው ነው፡፡
የትምህርት መስኮቹ መዘጋት ለዩኒቨርሲቲውም፣ ለአካባቢው ማኅበረሰብም ሆነ ለሀገር ብክነት ነው፡፡ በመሆኑም ጉዳዩ የሚመለከተውና የሚገደው ማንናው ሰው የሚከተሉትን ነጥቦች ሊያጤናቸው ይገባል፡፡
• ከሚዘጉት የትምህርት ክፍሎች ውስጥ አንዱ የሆነው አማርኛ የሃገሪቱ የሥራ ቋንቋ ከመሆኑም ባሻገር በመላ ሃገሪቱ የንግድ፣ የባህል፣ የትምህርት ቋንቋ መሆኑ፤
• በአማርኛ ትምህርት ክፍል ከሚጠቀሱት የጥናት መስኮች ውስጥ የግእዝ ጥናት አንዱ ነው፡፡ ይህ የግእዝ ቋንቋ ደግሞ ከጥንት ዘመን በተለይ መካከለኛው ዘመን ጀምሮ የሃገሪቱ ፖለቲካ፣ የባህል፣ የሥራ፣ የሥነ ጽሑፍ እና ኪነ ጥበብ ቋንቋ ሆኖ የዘለቀ መሆኑና መዘጋቱ የራሱ የሆነ ትውልዳዊ ክፍተት የሚፈጥር መሆኑ፤
• ከሚዘጉት የትምህርት ክፍሎች ውስጥ አንዱ ታሪክ በተለይ የመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ታሪክ ከሚጠናባቸው ሃሳባዊ ቦታዎች አንዱ የሸዋ አካባቢ መሆኑ ይታወቃ፡፡ የኢትዮጵያ የመካከለኛው ዘመን ታሪክ ዋነኛ ሁነቶች የተከናወኑበትና ከፍተኛ የጥናት ግብዓትና ሪሶርስ ያለበት አካባቢ ላይ ዩኒቨርሲቲው እንደመመስረቱ ይህን የጥናት መስክ ዋነኛ ትኩረቱ ሊያደርገው በተገባ ነበር፡፡

በ አቴና ቱማ አሳምነው

Check Also

ሻለቃ ውብ አንተን ስሙት።

በአሜሪካን ሀገር የምትኖሩ የአማራ ማህበራትና የአማራ ልጆች የት ነው ያላችሁት?? Share!

News in Pictures

Time in Ethiopia

Multi threaded Redundant Dedicated Server in USA and in Europe.