Breaking News
Home / Amharic / ሕዝቡን ጎዳና ላይ ጥለው ቤተመንግስት እየገነቡ ነው ::

ሕዝቡን ጎዳና ላይ ጥለው ቤተመንግስት እየገነቡ ነው ::

በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተሞች እየተካሄደ ነው ባለው የቤት ፈረሳ እና የግዳጅ የማስነሳት ሂደት 111 ሺህ 811 ቤቶችን አቶ ሽመልስ አብዲሳ ማስፈርሳቸውን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) አጋለጠ ።

ኢሰመጉ ይህንን የገለጸው ከጥቅምት 2015 ዓ.ም. ጀምሮ በጉዳዩ ላይ ያካሄደውን የምርመራ ሪፖርት ግንቦት 23/2015 ዓ.ም. ይፋ ባደረገበት ጊዜ ነው።

ኮሚሽኑ ይህንን አሃዝ ይፋ ያደረገው በአዲስ አበባ እና በሸገር ከተሞች ከሚኖሩ ነዋሪዎች የደረሰውን አቤቱታ፣ እንዲሁም አቤቱታ አቅራቢዎች በተወካዮቻቸው በኩል ያቀረቡት መረጃዎች መሠረት በማድረግ ነው።

ባለሥልጣናት ሕገወጥ በማለት ባካሄዱት የማፍረስ ድርጊት ከመኖሪያ ቤቶች በተጨማሪ የእምነት ተቋማት መፍረሳቸውንም ሪፖርቱ አመልክቷል።

ኢሰመጉ ከኦሮሚያ ክልል የእስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት አገኘሁት ባለው የቃል መረጃ መሠረት ከ19 በላይ መሰጂዶች መፍረሳቸውን ጠቅሷል።

ኢሰመጉ በዚህ ሪፖርቱ በርካታ ቦታዎችን ላካሄደው የምርመራ ሥራው መሸፈኑን አስታውቋል።

ከእነዚህም መካከከልም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና በኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ አስተዳደር ውስጥ የሚገኙ ኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 03 ልዩ ስሙ ሌንጮ ሰፈር፣ ማርያም ሰፈር እና ፋኑኤል ቤተክርስቲያን ሰፈር ይገኙበታል።
በተጨማሪም በየካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ አንቆርጫ ገብርኤል፣ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 በተለምዶ አሳማ እርባታ፣ ለገጣፎ ለገዳዲ 44 ማዞሪያ፣ ለገዳዲ የውሃ ግድብ ኬላ እና ሥላሴ እንዲሁም ኦሮምያ ክልል አዳማ ከተማ ቦኩ ሸነን ተጠቅሰዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በኦሮሚያ ክልል የሸገር የከተማን ጨምሮ ከ600 በላይ ከተሞች ሕገወጥ የቤት ግንባታ ላይ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ ረቡዕ ግንቦት 23/ 2015 ማስታወቃቸውን የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

የከተሞችን ፕላን ለማስጠበቅ እና በሕገወጥ መልኩ የተያዙ መሬቶችን ለማስመለስ አቅዷል በተባለው በዚህ ፈረሳ፣ ሕገወጥ ግንባታ አስፋፍተዋል የተባሉ አመራሮችም በሕግ ተጠያቂ ይሆናሉ ተብሏል።

እነዚህ ፈረሳዎች ብሔር እና ሃይማኖት ላይ ያነጣጠረ ነው መባሉን አስመልክቶ ምላሽ የሰጡት አቶ ኃይሉ፣ ሕግን እና ሥርዓትን በተከተለ መልኩ እየተከናወነ እንደሆነ እንዲሁም ሕገወጥ ቤቶች ላይ ያነጣጠረ ብቻ መሆኑን ገልጸዋል።

ኢሰመጉ በበኩሉ የቤት ፈረሳው የተለያዩ ቤቶችን እንደሚያካትት እና ከእነዚህም መካከል የባለይዞታነት ማስረጃ (እንደ አየር ካርታ) ያላቸው ቤቶች መካተታቸውን ገልጿል።

በተጨማሪ ከፈረሱት መካከል ከገበሬ ላይ በኢመደበኛ መልኩ የተገዙ መሬቶች ላይ የተሰሩ ቤቶች፣ አዋጅ ቁጥር 721/2004 ከመውጣቱ በፊት የተያዙ እና ግንባታ የተደረገባቸው ቤቶች (ከእነዚህም መካከል በሕጉ መሠረት ወደ መደበኛ ይዞታነት እንዲዞሩ ከመንግሥት አካላት ጋር ሲነጋገሩ የነበሩ እና በመጠባበቅ ላይ የነበሩ) እንደሚገኙበት ተካትቷል።

በተጨማሪም “በተሳሳተ ፖሊሲ ላይ የተመሰረተ፣ ወቅታዊነትን ያላገናዘበ፣ አማራጭ መፍትሄዎችን ያላካተተ፣ በአድሏዊ መንገድ እየተፈፀመ ያለ እና ብዙ ሺህ ዜጎችን ለማበኅራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ያጋለጠ ሕገወጥ ተግባር” ነው ሲልም ኮንኖታል።

“በሸገር ከተማ ብዛት ያላቸው መስጊዶች፣ ቤተ ክርስቲያኖች እና የፕሮቴስታንት ቤተ እምነቶች የሃይማኖት መብቶችን በሚዳፈር እና የአማኞችን ክብር በሚነካ መንገድ በአፍራሽ ግብረ ኃይል በግዳጅ እንዲፈርሱ ተደርገዋል” ብሏል።

Check Also

ሻለቃ ውብ አንተን ስሙት።

በአሜሪካን ሀገር የምትኖሩ የአማራ ማህበራትና የአማራ ልጆች የት ነው ያላችሁት?? Share!

News in Pictures

Time in Ethiopia

Multi threaded Redundant Dedicated Server in USA and in Europe.