#የምርመራዘገባ በአዲስ አበባ ኢሚግሬሽን ቢሮ በጉቦ ፓስፖርት የማውጣት ሂደት በማስረጃ ሲጋለጥ
– አንድ የሲስተም አድሚን ትናንት ብቻ በመመሳጠር 149 ፓስፖርቶችን ሰርቶ 745,000 ብር አግኝቷል
(መሠረት ሚድያ)- ፓስፖርት በጉቦ ማውጣት አሁን አሁን ህጋዊ እስኪመስል የተለመደ ሆኗል፣ የሚመለከታቸው አካላትም ጉዳዩ የእነሱ እስከማይመስል ድረስ ችላ ያሉት ይመስላል።
የተወሰኑ የኢሚግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት ሰራተኞችና ደላሎች ተመሳጥረው ድርጊቱ ላይ መሰማራታቸውን መሠረት ሚድያ ከዚህ በፊት ባደረጋቸው ማጣራቶች አረጋግጦ ነበር።
የኢምግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ለአስቸኳይ ፓስፖርት ለ 2 ቀን ቀጠሮ 25 ሺ ብር፣ ለአምስት ቀን ቀጠሮ 20 ሺ ብር በማስከፈል በኦንላይን በሚሞላ ፎርም አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ይታወቃል፡፡
ተቋሙ ሲስተሙ ይሰራል በማለት ለህዝብ ቢያሳውቅም ኦንላይን የሚሞላው ፎርም ግን በማንኛውም ጊዜ ሲከፈት ‘There is no available appointment date, Please check Later!’ የሚል ጽሁፍ እያመጣ እየሰራ እንዳልሆነ ማንም ማረጋገጥ የሚችለው ሀቅ ነው፣ ይህ ደግሞ ለወራት የዘለቀ ችግር እንደሆነ ይታወቃል።
አሁን ላይ ከተቋሙ ግቢ ውጪ ያሉ አካላት እና የኢሚግሬሽን ሰራተኞች ተመሳጥረው ለአስቸኳይ ፓስፖርት እስከ 35 ሺህ ብር እያስከፈሉ ሲሆን በተቋሙ ውስጥ ከሚሰሩ አንዳንድ የአይቲ ባለሙያዎች ጀምሮ እስከ አመራሮች የሚሳተፉበት ኔትወርክ በመዘርጋት ሲስተሙን ከእነርሱ ጋር ተመሳጥረው የሚሰሩ ግለሰቦች ብቻ ማግኘት እንዲያደርጉ በማመቻቸት ዜጎችን እየበዘበዙ ይገኛሉ፡፡
መሠረት ሚድያ አዲስ አበባ በሚገኘው ዋናው የኢሚግሬሽን ቢሮ የሚሰራው ይህ ህገወጥ አሰራርን ተመልክቷል።
ጉዳዩ እንዲህ ነው፣ አስቸኳይ ቀጠሮ የሚባለው አገልግሎት አሁን ላይ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ተዘግቶ የኢሚግሬሽን ሰራተኞች የሆኑ የተቋሙን ሲስተም አድሚን (admin) የሚቆጣጠሩ ሰራተኞች በውስጥ መስመር ከደላሎች ጋር በመመሳጠር ህዝቡን 35,000 ከተቀበሉ በኋላ እነዚህ አድሚኖች ከ5,000 ብር እስከ 6,500 ብር ይቀበላሉ።
ይህን የሚያሳይ አንድ ቪድዮ የደረሰን ሲሆን (ስክሪንሾቱ ከዜናው ጋር ተያይዞ ይታያል) አንድ የተቋሙ አድሚን ብቻ በአንድ ቀን የ149 ሰዎችን ፋይል ብቻውን እንደሰራ ያሳያል፣ ይህም ማለት በአንድ ፓስፖርት 5,000 ብር ሂሳብ በቀን 745,000 ብር ያገኛል ማለት ነው።
ድረ-ገፁ ለህዝብ ዝግ ተደርጎ እንዲህ ውስጥ ለውስጥ የሚሰራው የፓስፖርት ብዛት ከፍተኛ መሆን አዲስ መረጃ ባይሆንም በዚህ መጠን አንድ ግለሰብ ብቻ ገንዘብ በህገወጥ መንገድ ማግኘት መቻሉ ለምን ችግሩን መቅረፍ እንዳልተፈለገ ማሳያ ነው።
አንዳንድ ግለሰቦች በትናንትናው እለት ብቻ በርካታ መቶ ሺህ ብሮችን ከፍለው የበርካታ ግለሰቦችን ፓስፖርት አዲስ አበባ ካለው የኢሚግሬሽን ቢሮ እንደተቀበሉ ያገኘነው መረጃ ያሳያል።
በኢሚግሬሽን ሰርቨር ላይ ተቀምጠው ይህን ድርጊት የሚፈፅሙት አካላት ከሚያገኙት ገንዘብ ላይ ለበላይ አመራሮች ያካፍሉ እንደሆን በአንድ ወቅት የጠየቅናቸው አንድ የተቋሙ ሰራተኛ “ካለ እውቅና እና ካለ ቡጨቃ የሚሰራ ስራ የለም” የሚል አጭር ምላሽ ሰጥተው ነበር።
አቡ አብዱራህማን የተባሉ የመሠረት ሚድያ ፀሀፊ ከሰሞኑ ለሚድያችን ልከው ባቀረብነው ፅሁፋቸው “የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ከፓስፖርት ጋር ተያይዞ በህዝብ ላይ እየፈፀመ የቆየውና አሁንም አሻሽያለሁ እያለ በሪፖርት የሚለፍፈው ነገር ግን እንኳን ሊያሻሻል ዘረፋው ዘምኖ ተጧጡፎ ቀጥሏል” ብለው ነበር።
አቶ አቡ አክለው አሁን ላይ ለፓስፖርት ቀጠሮ በኦላይን ፕላትፎርም አዘጋጅቶ ማህበረሰቡ ባለበት ቦታ በስልክ ወይም ኮምፒውተር ቀጠሮ ማስያዝና ለባዮሜትሪክ መረጃ ለመስጠት በቀጠሮ ቀን መቅረብ ብቻ እንዳለበት የታወቀና ሲሰራበት ነበር ያሉ ሲሆን ይሁን እንጂ አስቸኳይ ፓስፖርት በ2 ቀን 25,000 ብር እና የ5 ቀን 20,000 ብር እንደሆነ እየታወቀ ሲስተሙን ማህበረሰቡ እንዳይጠቀም በመዝጋት ቀጠሮ ሊያስቀጥር ቢሮ ሲሄድ “እዚህ አይቀጠርም፣ ውጪ ሂድና አስቀጥረህ በቀጠሮ ቀን ለአሻራ ብቻ ና” ይባላል ብለዋል።
“ውጪ በራሱ እንዳያስቀጥር ሲስተሙን ሎክ አድርገውታል፣ ውጪ እኛ እናስቀጥራለን የሚሉ ሰዎች አዘጋጅተው በእነሱ አማካኝነት የ2 ቀን 25,000 ብር የነበረውን እስከ 35,000 ብር፣ የ5ቀን 20,000 ብር የነበረውን እስከ 30,000 ብር ተቀብለው እነዛ ደላሎች ውስጥ ኢሚግሬሽን ለሚሰሩት መረጃ ልከው እንዲቀጥሩ ይደረጋል” በማለት ጉዳዩን አብራርተዋል።
“ህዝቡ ተሰቃየ፣ ለማረጋገጥ ማንም በተቋሙ ፕላትፎርም ገብቶ ‘Urgent Appointment’ ቀጠሮ ደጋግሞ መሞከር ይችላል። እነሱ ቢሮ ውስጥ ግን በገለፅኩት መልኩ ተመሳጥረው ይሰራሉ፣ የውሸት ሪፖርትና ዜና በየተቋማቱ መስማት ሰለቸን” ብለው ተናግረዋል።
መሠረት ሚድያ የተቋሙን አመራር በዚህ ዙርያ ለማናገር ተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግም አልተሳካም።
የኢምግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት በአገልግሎት አሰጣጡ ዙርያ በቅርቡ በፓርላማ አባላት ጭምር ከፍተኛ ወቀሳ እንደደረሰበት ይታወሳል።
መረጃን ከመሠረት!