የአብይ አህመድ አገዛዝ የአማራን ህልውና ተጋድሎ ለማዳከም የነደፈው የመጨረሻው የሴራ መረብ ታወቀ!
የአብይ አህመድ አገዛዝ በአማራ ህዝብ የህልውና ተጋድሎና በፋኖዎች የአንድነት ጉዞ ዙሪያ የደረሰበትን ከፍተኛ ድንጋጤ ተከትሎ፣ የትግሉን አቅጣጫ ለማስቀየርና አንድነቱን ለመበተን የነደፈው አዲሱና ሚስጥራዊው የጥፋት ስልት ዝርዝር መረጃዎች ለዝግጅት ክፍላችን ደርሰዋል።
ይህ መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በአራት ኪሎ ቤተ-መንግሥት ውስጥ ሰሞኑን የተካሄደው ከፍተኛ ግምገማ በአገዛዙ ታሪክ ውስጥ ታይቶ የማይታወቅ የመርበድበድና የውሳኔ መደናገር የታየበት ነበር ተብሏል።
ላለፉት ዓመታት “ፋኖ በጎጥና በየአካባቢው ተከፋፍሎ አይዘልቅም፣ አንድ ሊሆን አይችልም” በሚል የከንቱ ተስፋ ስሌት ውስጥ ተዘፍቆ የነበረው የአብይ አህመድ አስተዳደር፣ ዛሬ በምድር ላይ የታየው እውነታ ከህልሙና ከግምቱ በላይ ሆኖበታል። የአማራ ፋኖዎች ሁሉንም ሰው ሰራሽ መሰናክሎች ጥሰው ወደ አንድ ጠንካራ ድርጅታዊ መዋቅርና ወታደራዊ ዕዝ መምጣታቸው፣ በአገዛዙ ሰማይ ስር ለተቀመጡት ባለስልጣናት የሞት አዋጅ ያህል ከብዷቸዋል ሲል አንድ በስብሰባው የተሳተፈ የአገዛዙ አመራር ለኢትዮ 251 ሚዲያ መረጃውን ተናግሯል።
በዚሁ ሚስጥራዊ ግምገማ ላይ በግልጽ እንደተነገረው፣ አገዛዙ ቀደም ሲል “ኃይል አለን” በሚል ስም በየሆቴሉ ድግስ ሲደግስላቸውና የአየር ላይ የፖለቲካ ትርፍ ሲያሰላባቸው የነበሩ፣ ነገር ግን በምድር ላይ ምንም አይነት ወታደራዊ አቅም የሌላቸው የፋኖ ስምሪቶች ሙሉ በሙሉ የከሰሩ ሆነው ተገኝተዋል። አገዛዙ በከፍተኛ በጀትና በጥቃቅን ጥቅማጥቅሞች የደለላቸው እነዚህ ግለሰቦች፣ በተግባር ግን አንዲትም ክፍለ ጦር ቀርቶ አንድ ሺህ ፋኖን እንኳ ይዘው ወደ አገዛዙ ጎራ ሊቀላቀሉ አለመቻላቸው የቤተ-መንግሥቱን ባለስልጣናት ለከፍተኛ ንዴትና ብስጭት እንደዳረጋቸው የመረጃ ምንጫችን ገልጿል።
እንዲያውም “የእነዚህን ሰዎች የሆቴልና የሱስ ወጪ መሸፈን እንጂ ያተረፍነው የፖለቲካ ትርፍ የለም” የሚለው ይፋ ያልሆነው የግምገማው ውጤት፣ አገዛዙ በገንዘብ ሊገዛው የሞከረው ትግል በፅናትና በዕውነት ላይ የቆመ መሆኑን በግድ እንዲያምን አስገድዶታል ብሏል።
ይህ በምድር ላይ የደረሰበት ሽንፈትና የስትራቴጂ ክሽፈት ያላረካው የአብይ አህመድ አገዛዝ፣ አሁን ደግሞ የጥፋት መረቡን ወደ ውጭው ዓለምና ወደ ምሁራን ዘርፍ ያዞረ ሲሆን፣ ለዝግጅት ክፍላችን የደረሰው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በአገዛዙ የተቀመጠው አዲሱ አቅጣጫ በውጭው ዓለም የሚኖረው የአማራ ዲያስፓራና የፋኖ ደጋፊዎች ወደ አንድ ጠንካራ የገንዘብ፣ የሃሳብና የዲፕሎማሲ ጥላ ስር እንዳይመጡ ያለውን የመንግሥት አቅም ሁሉ ተጠቅሞ የማበላሸትና የመበተን ስራ እንዲሰራ ጥብቅ መመሪያ ወርዷል።
ዲያስፓራው የትግሉ የጀርባ አጥንትና የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ድምፅ መሆኑን የተረዳው አገዛዙ፣ ይህንን አቅም ለማዳከም የቆየውንና ያረጀውን “የጎጥ” አጀንዳ ዳግም እንዲያንሰራራ ለማድረግ የደህንነት መዋቅሩንና የማህበራዊ ሚዲያ ሰራዊቱን ሙሉ በሙሉ እንዲንቀሳቀስ አቅጣጫ ማስቀመጡን የመረጃ ምንጫችን ለጣቢያችን ተናግሯል።
የአማራ ተወላጆች በየትውልድ አካባቢያቸው ተከፋፍለው እርስ በርስ እንዲጠራጠሩ፣ አንዱ ሌላውን እንዲወነጅልና በጋራ ዓላማ ላይ እንዳያተኩሩ ለማድረግ ታቅዶ እየተሰራ ይገኛል። በተለይም ትውልደ ኢትዮጵያውያን የሆኑና ለትግሉ ትልቅ አቅም ሊሆኑ የሚችሉ ግለሰቦች እርስ በርስ እንዳይግባቡና ድምፃቸውን እንዳያቀናጁ የማሰናከል ስራው በከፍተኛ ደረጃ እንዲከናወን መመሪያ ተሰጥቷል ብሏል የመረጃ ምንጫችን።
ከዚህም በተጨማሪ፣ በአገዛዙ በኩል በምሁራን ላይ የታወጀው የጥፋት ዘመቻ እጅግ አደገኛና ኢ-ሰብአዊ በሆነ መልኩ ተቀርጿል። የአማራ ተወላጅ የሆኑ ምሁራን ፋኖ አንድ ከሆነ በኋላ በጋራ ለመስራትና ትግሉን በዕውቀት ለመደገፍ እያደረጉት ያለው እንቅስቃሴ ለአገዛዙ የመጨረሻው አስፈሪ ህልም ሆኖበታል። በመሆኑም እነዚህን ምሁራን በማህበራዊ ሚዲያ የመሳደብ፣ የማሸማቀቅ፣ ስማቸውን የማጥፋትና የማነወር ስራ በስፋት እንዲሰራ መመሪያ እንደተላለፈ ለኢትዮ 251 ሚዲያ መረጃውን ያደረሰው አመራር አክሎ ገልጿል።
የመረጃ ምንጫችን እንደነገረን ከሆነ፣ አገዛዙ ምሁራኑን ከትግሉ እንዲርቁና እንዲፈሩ ለማድረግ “ከፍ ካለም ማሰርና መግደል” የሚል እጅግ አደገኛና ፋሽስታዊ አቅጣጫ አስቀምጧል። ይህ የምሁራን አደን ዘመቻ፣ አገዛዙ በዕውቀትና በስትራቴጂ የሚመራን ትግል ምን ያህል እንደሚፈራ ቁልጭ አድርጎ ያሳያል። ምሁራኑ ለትግሉ የሚሰጡት የሞራልና የስትራቴጂ ድጋፍ የአገዛዙን የውሸት ትረካዎችና ፕሮፓጋንዳዎች ስለሚያፈርስባቸው፣ እነዚህን የህዝብ አይኖች ለማጥፋትና ድምፃቸውን ለማጥፋት ቆርጠው ተነስተዋል ብሏል።
ይህንንም ሰፊና ውስብስብ የሴራ ዘመቻ በበላይነት እንዲመራውና በየቀኑ ክትትል እንዲያደርግበት የታዘዘው ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ነው። ይህም ጉዳዩ ከአገዛዙ ህልውና ጋር በቀጥታ የተያያዘ መሆኑንና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራሳቸው የዚህ ጥፋት ቀጥተኛ መሪ መሆናቸውን የመረጃ ምንጫችን አረጋግጠውልናል።
ይህ የአገዛዙ አዲስ የጥፋት ስልት በአንድ በኩል ድክመቱን በሌላ በኩል ደግሞ የጥፋት ጥሙን በግልጽ ያሳያል። “ፋኖ አንድ አይሆንም” የሚለው ግምገማቸው መክሸፉ፣ ህዝባዊ ትግልን በሴራና በገንዘብ ለመቆጣጠር መሞከር እንደማይቻል ትልቅ ትምህርት በሆነ ነበር። ነገር ግን አገዛዙ ከታሪክ ስህተቱ ከመማር ይልቅ፣ ይበልጥ ወደ ኃይልና ወደ ስር ነቀል ጥፋት አዘንብሏል ሲል የመረጃ ምንጫችን ትዝበቱን አክሎ ገልጿልናል።
በውጭ ያለውን ዲያስፓራ ለመበተን የሚደረገው ጥረት፣ በአገር ውስጥ ያለውን ምሁር ለማጥፋት የታወጀው አዋጅና የጎጥ ፖለቲካን ዳግም ለማንገስ የሚደረገው ሩጫ ሁሉ የአንድ እየወደቀ ያለ ስርአት የመጨረሻ ትንፋሾችና የመጨረሻ የጥፋት ካርዶች ናቸው። የአማራ ህዝብና ፋኖ የደረሱበት የአንድነት ደረጃ ለኢትዮጵያ ህዝብ ተስፋን፣ ለአገዛዙ ደግሞ መርዶን ይዞ መጥቷል። ቤተ-መንግሥቱ በሴራ መረብ ተጠምዶ የአማራን ልጆች ደም ለማፍሰስና አንድነታቸውን ለመበተን ቢመክርም፣ በፅናትና በአላማ የተሳሰረን ትግል በምንም አይነት ምድራዊ ኃይል ሊገታው እንደማይችል መላው የኢትዮጵያ ህዝብና ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ሊገነዘበው ይገባል ሲል የመረጃ ምንጫችን ጨምሮ ለጣቢያችን ገልጿል።
ኢትዮ 251 ሚዲያ
የነጻነት አንደበት!
Amhara Fano Supporters – የአማራ ፋኖ ደጋፊዎች Amhara Fano Support Website – የፋኖ ደጋፊዎች
