ለዓመታት ውጊያ ሲያካሂዱ የነበሩት የሶሪያ አማጺያን መዲናዋ ደማስቆን መቆጣጠራቸውን እና ከፕሬዝዳት ባሻር አል-አሳድ ከአገሪቱ መሸሻቸውን አስታወቁ።
የሶሪያ መንግሥት ኃይሎችም ከዋና ከተማዋ እንደሸሹ እና አማጽያን በቁጥጥራቸው ሥር እንዳዋሏት ገልጸዋል።
አሳድ ከደማስቆ ሸሽተው ወዳልታወቀ ሥፍራ በአውሮፕላን እንደሄዱ የሚጠቁሙ ሪፖርቶች ወጥተዋል።
‘ጨቋኙ’ አሳድ በመሸሹ ሶሪያ ‘ነጻ’ መሆኗን አማጽያኑ በይፋ አውጀዋል።
ሮይተርስ የዜና ወኪል ሁለት የሶሪያ መንግሥት ባለሥልጣናትን አነጋግሮ እንደዘገበው፣ ፕሬዝዳንቱ መዲናዋን ለቀው ሸሽተዋል።
የአማጺ ቡድኑ ኤችቲኤስ ተዋጊዎች ወደ መዲናዋ መግባታቸውን ከገለጹ በኋላ በሺዎች የሚቆጠሩ ተቃዋሚ ፖለቲከኞችን የሚደግፉ እስረኞችን ከታሰሩበት ሳይንድንያ እስር ቤት እንዳስለቀቁ ተናግረዋል።
በዚህ እስር ቤት ተቃዋሚዎች እንደሚሰቃዩ እና እንደሚገደሉም ይነገራል።
የአሳድ ዋነኛ ደጋፊ በሆነችው ኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ ወታደሮቹን ከተወሰኑ አካባቢዎች አስወጥቷል።
አማጺያኑ የሶሪያ ሦስተኛ ትልቅ ከተማ የሆነቸው ሆምስን የተቆጣጠሩት ከቀናት በፊት ነው።
አማጺ ቡድኑ ኤችቲኤስ በቴሌግራም ላይ “ጨለማው ዘመን አብቅቶ አዲስ ጊዜ ተጀምሯል” ብሏል።
በአሳድ አስተዳደር የተፈናቀሉ ወደ ቤታቸው እንዲመለሱም አሳስቧል።
“ሁሉም ሰው በሰላም የሚኖርባት እና ፍትሕ የሚሰፍንባት አዲስ ሶሪያ ናት” ብሏል ቡድኑ።
በደማስቆ ማዕከል በሚገኘው ኡማያድ አደባባይ ሰዎች ደስታቸውን እየገለጹ ነው የሚሉ ሪፖርቶች ወጥተዋል።
በአካባቢው የመከላከያ ሚኒስትር ይገኛል።
ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የሚዘዋወሩ ተንቀሳቃሽ ምሥሎች ሙዚቃ ተከፍቶ ነዋሪዎች እየደነሱ ያሳያሉ።
ወታደሮች ታንኮችን ጥለው የሸሹ ሲሆን፣ ነዋሪዎችም በታንኮች ዙሪያ ሲደንሱ ታይቷል።
የሶሪያ መከላከያ ሚኒስቴር ባለሥልጣናት ደማስቆ ከሚገኘው ዋና መቀመጫ ሸሽተው መውጣታቸው ተገልጿል።
አማጽያኑ ሆምስ ከተማን ‘ሙሉ በሙሉ ነጻ አውጥተናል’ ማለታቸውን ተከትሎ ነው ወደ ደማስቆ ያመሩት።
የሶሪያ የተቃዋሚ መሪ ሀዲ አል-ባሕራ “የሶሪያ ጨለማ ዘመን አከተመ” ሲሉ አል-አረቢያ ለተባለ መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።
ናሽናል ኮአሊዥን ኦፍ ሲሪያን ሪቮሉሽን ኤንድ ኦፖዚሽን ፎርስስ የተባለው ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የሆኑት አል-ባሕራ እንዳሉት፣ በደማስቆ የነዋሪዎች ደኅንነት የተጠበቀ ነው።
“በሁሉም ሃይማኖት እና ቡድን ውስጥ ያሉ ዜጎቻችን ከዚህ በኋላ እርስ በእርስ መዋጋት የለባቸውም። ቤታቸው እስከሆኑ ድረስ ደህና ናቸው። በቀል አይኖርም። ሰብአዊ መብትም አይጣስም። የሰዎች ክብር ይጠበቃል” ሲሉ በኤክስ ገጻቸው ጽፈዋል።