“ወታደሮቹ፣ የዚህች እናት ብቸኛ ልጅ የሆነውን ወጣት ከገደሉት በኋላ፣ እናቲቱን ወደ ልጇ አስከሬን አስጠጉ። በዚያም አልቆሙም፤ እኚህ እናት በገዛ ልጇ ሬሳ ላይ ወደ ፊት እና ወደ ኋላ እየዘለሉ እንዲረማመዱ አስገደዱአቸው።”
የሚከተለው የህይወት ምስክርነት፣ ከሞት አፋፍ ተርፎ ለታሪክ የመዘገበው የጎይቶም መኮንን እውነተኛ ገጠመኝ ነው። ጎይቶም፣ በጦርነቱ ወቅት ያሳለፈውን ሲኦል የመሰለ ህይወት፣ “Primed for DEATH” በሚል ርዕስ በፃፈው መጽሐፉ በዝርዝር አስፍሮታል። ይህ ታሪክ በመጽሐፉ ውስጥ በስፋት የተካተተ ሲሆን፣ ለጋዜጠኛ ናታሊ ሶሳ በሰጠው ቃለ-መጠይቅም ላይ የዚህን መጽሐፍ አንኳር እና ልብ ሰባሪ ገጠመኞች አጋርቷል።
በሐበሻ ብሮድካስት ተተርጉሞ የቀረበ
የደም እንባ በአክሱም፡ የማይሽር የህሊና ጠባሳ እና የሰቀቀን ትውስታዎች
በኖቬምበር 2020 በአክሱም ከተማ የተከሰተው እልቂት፣ የሰው ልጅ በሰው ልጅ ላይ ሊፈጽመው የሚችለውን የጭካኔ ጥግ ያሳየበት የታሪክ ምዕራፍ ነው። ጎይቶም፣ በአክሱም የጽዮን ማርያም ዓመታዊ በዓል ዋዜማ እና ዕለት በሆነው በኖቬምበር 28 እና 29 የተመለከተው የሞት ጥላ፣ ቃላት ሊሸከሙት ከሚችሉት በላይ ከባድ ነው።
የሬሳ ክምር እና የጋሪው ጉዞ
በእነዚያ ቀናት አክሱም የሙታን ከተማ መስላ ነበር። ጎይቶም እንደመሰከረው፣ የከተማዋ ጎዳናዎች በንፁሃን ዜጎች አስከሬን ተሞልተው ነበር። የሟቾቹ ቁጥር እጅግ ከፍተኛ ከመሆኑ የተነሳ፣ በሰው ጉልበት ተሸክሞ ለመቅበር የሚታሰብ አልነበረም። ነዋሪው፣ በአሰቃቂ ሁኔታ የተገደሉትን ወገኖቹን አስከሬን ለመሰብሰብ ጋሪዎችን ለመጠቀም ተገደደ። በየመንገዱ የወደቀውን የሰው ልጅ አስክሬን ክብር አልባ ሆኖ ሲመለከት፣ የሞት ሽታው አየሩን ሲሞላው፣ ጎይቶም ከዚህ ጦርነት በህይወት ተርፎ እንደሚወጣ እርግጠኛ አልነበረም።
የእናት ሰቀቀን፡ የጭካኔው ሁሉ ቁንጮ
ከሁሉም በላይ የጎይቶምን ልብ በሃዘን የሰበረው እና የሰው ልጅ ህሊና ሊቀበለው የሚከብደው ድርጊት፣ የኤርትራ ወታደሮች በአንዲት እናት ላይ የፈጸሙት ግፍ ነው። ይህ ድርጊት የጭካኔን ትርጉም የሚቀይር ነበር። ወታደሮቹ፣ የዚህች እናት ብቸኛ ልጅ የሆነውን ወጣት ከገደሉት በኋላ፣ እናቲቱን ወደ ልጇ አስከሬን አስጠጉ። በዚያም አልቆሙም፤ እኚህ እናት በገዛ ልጇ ሬሳ ላይ ወደ ፊት እና ወደ ኋላ እየዘለሉ እንዲረማመዱ አስገደዱአቸው። አንዲት እናት፣ አምጣ በወለደችው እና የዓይኗ ብሌን በሆነው ልጇ አስከሬን ላይ እንድትረማመድ መደረጉ፣ ስጋዊ ሞት ብቻ ሳይሆን የመንፈስ እና የህሊና ግድያ ነበር። ይህ ክስተት በጎይቶም አእምሮ ውስጥ እንደማይጠፋ ምስል ተቀርጾ ቀረ።
የፍጹም አሳዛኝ ፍጻሜ
ጎይቶም በተጠለለበት ሆቴል ውስጥ አብሮት የነበረው ፍጹም የተባለ ወጣት ታሪክም ሌላው የልብ ስብራት ነው። ፍጹም፣ በሆቴሉ ውስጥ የሚሰራ ወጣት ነበር። ለአራት ቀናት ያህል በሆቴሉ ክፍል ውስጥ ተዘግቶባቸው ሲቆዩ፣ ለሁለት ቀናት ያህል ምንም ዓይነት ምግብ አልቀመሱም ነበር። ረሃቡ ሲጠናበት፣ ፍጹም ሁኔታዎችን ለማጣራት ወደ ውጭ ወጣ።
በዚህ ጊዜ፣ አንዳንድ የኤርትራ ወታደሮች የድሮውን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የደንብ ልብስ ለብሰው ነበር። ይህ ማታለያ፣ ፍጹምን አሳሳተው። የትግራይ ኃይሎች የመጡ መስሎት ወደ ጓደኞቹ ተመልሶ “ወታደሮቹ ወደ ሌላ አቅጣጫ ሄደዋል” የሚል ተስፋ ሰጣቸው። ነገር ግን ተመልሶ ሲወጣ ያጋጠመው ሞት ነበር። ወዲያውኑ የተኩስ ድምፅ ተሰማ፤ ፍጹምም አልተመለሰም።
በማግስቱ ጠዋት፣ ጎይቶም የፍጹምን አስከሬን ከሆቴሉ አጠገብ ወድቆ አገኘው። ደሙ መሬቱ ላይ እና ልብሱ ላይ ደርቆ ነበር። ለሁለት ቀናት በረሃብ ሲሰቃይ የነበረው ያ ወጣት፣ በዚህ አሳዛኝ ሁኔታ ህይወቱ አለፈ። ጎይቶም፣ “ምነው ባልወጣ ኖሮ፣ ምነው ህይወቱን የምናተርፍበት ዕድል አግኝተን በሆነ” እያለ በፀፀት ሲቃጠል ይኖራል።
የቤተሰብ እልቂት እና የእህት ሰቀቀን
ይህ ጦርነት ጎይቶምን በግልም አላለፈውም። በዚህ ጭካኔ በተሞላበት ወቅት፣ ታናሽ ወንድሙን አጣ። ወንድሙ በተገደለበት ቅጽበት፣ ታናሽ እህቱ አብራው ነበረች። እሷም እጅ እና እግሮቿ ላይ ከባድ የመቁሰል አደጋ ደረሰባት። የእህቱ ሰቀቀን ግን ከቁስሉ በላይ የከበደ ነበር። የምትወደው ወንድሟ በወታደሮች ሲገደል በዓይኖቿ ፊት ተመልክታለች። ጎይቶም ስለዚህ ሲናገር፣ “እኔ ለአንድ አፍታ ብቻ ባየኋቸው ሰዎች ሞት እንዲህ ከታመምኩ፣ ወንድሟ ዓይኖቿ ስር ሲገደል ያየችው እህቴ ህመሙ እንዴት ይቻላት ይሆን?” ሲል ይጠይቃል። ይህ ጥያቄ፣ ከጦርነቱ የተረፉት ሰዎች የሚሸከሙትን ዘላለማዊ የህሊና ቁስል ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው።
Amhara Fano Supporters – የአማራ ፋኖ ደጋፊዎች Amhara Fano Support Website – የፋኖ ደጋፊዎች